Thursday, December 12, 2013

ጠርዝ ላይ ያለ ስጋቴ – በመንትዮሽ። ከሥርጉተ ሥላሴ


ከሥርጉተ ሥላሴ
12.12.2013
ስጋት እንደሚፈቀድልኝ አስልቼ ሃሳቤን ንፉግ ሳልሆን ልገልጽ ወሰንኩ። መወሰንና መቁረጥ መልካም ናቸው። ካሰቡት
የሚያድርሱ ሰጋሮችና ገሮችም።
andu-family-45
በሌላ በኩልም ከመንፈስ መታከት ይታደጋሉ – ይመስለኛል። እመቤት ነፃነትና ፊታውራሪ ሂደት እውኃ በሚያደርግ ፋስ ለማን አዘነሉት?! የፊታውራሪ ሂደት የትርታ – ትብብር አማ ስንቱን ገበርዲን ስንቱን ሙሉወርድ ዋጠው? ስንት አቅም ባከነ – ስንት ፍቅርስ አለቀሰ? ስንት አብሮነትስ ተከፋ? ሰረዘው … ሰወረው? ፊታውራሪ ሂደት ብዙም ሳንርቀው ግራው – ቀኙ – ማዕከላዊነትን አግቶ ወይንም ነካክቶ። የቅርቡን ስናስበው ሁለት ምርጫ ይዞ ቀረቦ ነበር። ዘንባባ ወይንስ ሳንጃ በማለት አሳፈን። እኔ ከአጠው ቋጥኝ አፋፍ ላይ ሆኜ ናዳውን ለእህትና ወንድሜ፤ እህትና ወንድሜም አጸፋውን በመልቀቅ ተጠን። የባሰው ግን ሺዎች አለፉ፤ በእስር ማቀቁ … ስንት የፍቅር ቤት – ትዳር ተፈታ፤ ተናደ ~~~ አብሶ ህፃናት የወላጅ ናፍቆት አሰቃያቸው፤ ፍቅርና እንክብካቤ አጥተው ቀጨጩ። ኢዲህቅ፣ አማራጭ፤ ህብረት፤ ቅንጅት ….
ቅንጀት እራሱ ኢዲአፓ፤ አላይንስ፤ ግንቦት፤ አንድነት፤ መድረክ፤ ጥምረት፤ ዝም አንልም፤ ግንቦት ዲ፤                   የጥቃቱ ሰለባዎች በፋመ በቀል እዬተቀቀጡ ያሉ- የነገ ትውልድ ተስፋዎች ትብብር …. ያንተ ያለህ …. መከታከት ምዕራፋችን
ዬት ላይ ይናጠጥ ይሆን? …
ሎቢያችን በመደማመጥ የሚሰክነውስ መቼ? መንፈሳችን ከቋሳ ጸድቶ የጸዳ ማግሥት መቼ ይሆን ልደቱ? ክብሮቼ … በመኢህድ ዙሪያ ቢሆን በሥነ ደንብ ፊርማ ግብግብ የነበረውንም ታውቁታላችሁ። አንዲት ብሄራዊት ሀገር – በህብረ ቀለም ያጌጠች፤ አንድ የነጠረ ግን በብዙ የራቀን ፍላጎት የሰነቀ የነፃነት ራዕይ፤ አንድ መነሻ – አኃቲ መዳረሻ፤ ትርጉም ሰጥና አጉራሽ ጉዞ ተከትሎ ስንጥቅ ትርትር ገጠመኝ። ያደክማል። …. እህህህ …
ባለፉት ሳምንታት አንድነት ከመኢህድ ጋር አብሮ ለመስራት አንድ እርከን ላይ መድረሱን አነበብኩ።
ተከትሎም ብቸኛው የፓርላም አባልና የነፃነት ፈላጊ ቤተሰብ አባል የሆኑት አቶ ግርማ ሰይፉ „ኡ ኡ የመደማጥ ያለህ“ በሚል እርእስ ከዘመንተኞች ጋር አብሮ ስለመሰራት አለልስ ምኞታቸውን ከማሳሰቢያ ጋር አካፈሉን። ለማጣፈጫ አንድነት የአደራ መክሊትን ተግባር ላይ በማዋል ላይ ስለሚገኘው አቶ አንዱዓለም አራጌ የመጸሐፍ ምርቃ ላይ ሥርዓት አዘጋጅቶ አደባባይ በስሙ እንዲሰዬም ፍላጎቱን ነገረን። እንደ መዳረሻ ደግሞ ከኢሳት አንድ ሰበር ዜና አዳምጠን … ያው ዘኃ ግራው በአንድነት ዙሪያ ነው …
እኔ ልዩ ስጋት አደረብኝና … ሁኔታውን እንዲያብራሩልኝ ለተከበሩ ለአቶ ግርማ ሰይፉ ኢሜል አድራሻቸውን ከጹሑፋቸው ሥር ስላገኘሁት ቁልጭ ያለቸውን ስጋቴ ቅልብጭ ባለች አጭር ሀተታ ቋጭቼ ላኩላቸው። ቀኑ ነበር። መልሱን እዬጠበቅኩ ነው። ከትቢያም ይሁን ከጭድ ከታችኛው ክፍል የሚመጡ ቀና ዕይታዎች የነገ የተስፋችን መሪ ከሆኑት ይገኛል በማለት እዬጠበኩ ነው። መቼም ነፃነት የራበው የነፃነት ንፉግ እንደማይሆን በመስላት።
ትናንት – ደግሞ የሞቀ – የሰከነ – ጥልቅ – ተቆርቃሪነትን ያቀለመ መልእክት ከአደራ ጽኑ ጠበቂያችን ከአቶ አንዱዓለም አራጌ ዘሃበሻ ላይ አነበብኩ። ስጋቴም በዚህ ጥግ ዙሪያ ነበር። ለተከበሩ አቶ ግርማ ሰይፉ የፃፍኩትም ይኽንኑ የሙጥኝ ያለ ነበር። ልምዱ አለና። ክብረት ዳኛ ብርቱካን ሜዴቅሳ እስር ቤት ላይ ሁና ነበር አንድነት በአዲስ መልክ የማጠናከሪያ ምርጫ ያደረገው። እንዲሁም መድረክ የተወለደው። ስጋቴ ቅርንጫፍ ሳይሆን ሥር ያለው ነው። ፊታውራሪ ሂደት በበለኃሰብ እጅ፤ ካቴና ላይ ሆና ክብርት ዳኛ ብርቱካን ሜዴቅሳ ያገለለ ድራማ ከወነ አንድ መጋረጃ። ያን ጊዜ  „ዝም አንልም“ የሚል አንጃ በአንድነት ውስጥ ተፈጠረ። ከዚህ ሁሉ በላይ ስደት ላይ የምንገኘው በክፉም በደገሙ የምንገናኝ የእትብት ልጆች የፊታውራሪ ሂደትን ሃዲድ ተከትሎ በመጣው ጦስ በኢትዮጵውያን የመወያያ የጋራ ቤታችን ስንፋጭ እስከ መለያዬት አደረሰን። ሙጃው ወያኔም አራት ኪሎ ተራራ ላይ ሆኖ ከበሮውን ደለቀ …. ሄሮድስ መለስም አፈር እንደቀራባቸው ሳይተነብዩ ፍልቅልቅ ብለው ሳቁብን – ፈነደቁ።
የተስፋችን ማህደር የነበረችው ክብረት ዳኛ ብርቱካን ሜዴቅሳ ለትውልዱ የመጀመሪያ ሴት በመሆን በአንድ ሀገራዊ የብሄራዊ ፓርቲ መሪ ስለነበረች የብቃቷን ጡት ወተት ለመቀለብ ቀን ስንቆጥር መክኖና ፈልሶ ቀረ። እኔ ረቂቅ ናፍቆት ነበረኝ። መድረክ ላይ በአካል ስላዬኋት እሳሳላትም ነበር። ህልሜ ግን ተኖ ቀረ። አንዲት የቆረጠች እርግጠኛ ሴት አዲስ ቡቃያ ወጣት፤ ከምንም ነገር ጋር ንክኪ የሌላት ሰንደቅን የታጠቀች ብቸኛ የነፃነት አርበኛ ያላስተናገደ የዴሞክራሲ ትግል ፍቺ የለሽ ቅልሞሽ ነበር ለእኔ። እሷ ከመፈታቷ በፊት ሁሉ ነገር ተከወነ። ስትፈታ መግቢያ ቤቷ ከውስጥ ተከርችሞ፤ አደራ ያስረከበቻቸው የአንድነት ቤተሰቦቿ ጉልቻቸውን በፋስ ፈረካክሰው፤ በጎሪጥ ዳርና ዳር ሆነው በእሳትና በቃጠሎ ታጥረው አገኘቻቸው … ምን ይሁን? መግቢያ ያጣቸው አብነት … እንደ ተዘጋባት … ጨርሱትን እኔ አቅም የለኝም። አቤቱ ድህነትህ መቼ ይሆን!
የእኔ ስጋት ምንጭ ይህ ነው። ትናት እነ – አቶ ሰዬ  ዘውድ ተድፍቶላቸው ብርቴን … ዛሬ ደግሞ እነ – አንባሳደር ስዩም አንዷለምን …. ይሆን – ይሆን? …. የፊታውራሪ ሂደት የማጥቃት ወቅቱ ተመሳሳይ ነው። ያው የምርጫ ዋዜማ። መደረክ ያን ጊዜ፤ ዛሬ መኢህድ፤ አቶ ሰዬ ትናት ዛሬ አንባሳደር ስዩም መስፍን። የሚኮረኩር ነገር አለው።  የሚመጠምጥ ነገር። ብርቴም እንደ ዛሬው እንደ አንዱዓለም ውዳሴ ይደረደርላት፤ ቅኔ ይዘርፍላት ነበር – በሁላችንም። አቡነዘሰማያት ተዘውትሮ ይደገምላትም ነበር። ስለሆነም የአደራ ዋቢው አቶ አንዱዓለም የዓመቱ ምርጥ ሰው ሆኖ መመረጡ የነገን የመታገያ ወርዱን ሊያጠበው ወይንስ ሊያሰፋው የትኛው ይሆን ቅዱ የቦዩ፤ ጥግ የሚያሳጣ ይሆንይሆን መዝሙሩ? ተንጠልጥሏል ስጋቴ …. ጭንቅን ታጥቆ – ትዝብትን ተሸክሞ – ተስፋ ማጣትን አርግዞ …. እግዚኦ ነው እግዚኦ!
በሌላ በኩል አያድርገው እንጂ አቶ አንዷለምን የሚያገል ሁኔታ ቢፈጠር እኛ እንደፈረደብን ጋ (ቡድን) ለይተን ደግሞ እንደ ትናንቱ መፋለጡን እንቀጥላለ? ይህም የመንትያው ስጋቴ ሥጋና ነፍስ ነው። የፊታውራሪን ሂደትን መርኃ ግብር ውስጥ ቼክ ማድረግ አለብን። እስከ መቼ በቆራጣና ቆልማማ አፍንጫው እዬዳነሰብን ይኑር?! ትርፍና ኪሳራውን እንመትረው። ጠቀሜታውን እንፈታትሽው። እንደ ኖርንበት ሁኔታ ይህ የታደለ የሽፍታ አስተዳደር ወያኔ በአገኘው የመተንፈሻ ጊዜ ተጠቅሞ የለበጣ ልጥፍ ድራማውን የሚከውንበት አዲስ ለም ማሳ እንዳናዘጋጅ ጠንቀቅ።
ስጋት ወጥሮኛል ~ መፈናፈኛ ነስቶ ያባትለኛል ~ ሰንጎ ይፈትለኛል። በዬጊዜው በሚከፋፈለው የኮርኒስ ግድግዳ እንኳን ሆኖ ደፋ ቀና የሚለው የነፃነት ፈላጊ ቤተኛ ዛሬም ሌላ ስንጠቃ ይጠብቀው ይሆን? ሌላ የመሬት ክፍፍል ዕጣ ፈንታ? እ! ከሁሉ የሚያሳዝኑኝ በተለይ ነጭ ሀገር ተወልደው የሚያድጉ ልጆች ደንበርና ወሰን በዬጊዜው እዬተሰራላቸው በፍልሰቱ መንደር ሰላም አጥተው ከአቻዎቻቸው ጋር አብረው እንዳያሳልፉ ተስፋቸውን ሲኦል መልቀቃችን ነው …. ተሳህለነ!
ውህደቱም ሆነ ጥምረቱ፤ አዲስ የማጠናከሪያ በሉት የማሟያ ሂደቱን እላይ ባሉት ተወስኖ ተግባራዊ ይሆናል። ታች ያለው አባል የሚሰማው አባል እንዳልሆነው ልክ እንደ እኛ በመግለጫ ነው። መግለጫውን ተከትሎ መለያዬት ሲመጣ ታች ያለው ወገን ነው በጠላትነት ተፈራርጆ ሲዋቃ ውሎ የሚያደረው።  እጅግ የማከብራችሁ መንፈሰቼ፤ የሀገሬ ልጆች ከእንግዲህስ ሞኝ አንሁን። የተስማሙት እነሱ ሲለያዩም እነሱ ብቻ ይሁኑ …። እኛ በምን እዳችን ነው በዬጊዜው እንዲህ እምንተረተረው። አለቅን – ሳሳን እኮ! ስደቱ የማይቻል ሸክም፤ በዛ ላይ ደግሞ በዬዕለቱ አጀንዳ ስንሰነጣጠቅ የምንገኘው …. ስለምን ነው? ረዳት ጠያቂ አልባ እኮ ፈለስን!
ክብሮቼ ልብ ልንለው – በማስተዋል ልንመረምረው የሚገባው ጉዳይን እንሰበው …. ከልብ ውስጣችን እባካችሁን በሞቴ እንምራው። ለምናምንበት አካል የምንችለውን እናድርግ። … ሃሳብን በሃሳብ እናታግል በመከባበር በሥልጡን ሁኔታ። ከዚህ በተረፈ እኛ ቢያንስ በስደት ተሳስብንና ተዛዝነን እንደ ተፈጥሯችን በአብሮነት እንኑር …. የሱባኤ ጊዚያችን በተመክሯችን ጥሪት እናበልጽገው። መሪዎቻችንም ቁርጣቸውን ሲያውቁ እነሱ መከባበርን አዝምረው፤ ፈርኃ ፈጣሪን ጥሪት አድርገው፤ መግባባትን አድምጥው፤ ለመቻቻል እጃቸውን ሰጥተው፤ ሁሉን ቻል በማድረግ ለኢትዮጵያዊነት ሊታገሉ ይችላሉ። አልበላም እያለ ለሚያስችግር ልጅ ብትባላ ብላ፤ ባትበላ ተዎው ሲባል፤ ራህብ ሲያኮራምቶ ለምኖ ይበላታል። እስኪ በዚህ መንገድ ደግሞ ይሞከሩ … መሪዎቻችን …
የፊታውራሪ ሂደት ከነቤተሰቡ ጥቃት ቀጥተኛ ሰለባ የሆነው የ አደራ ቤተኛ አቶ አንዱዓለም አራጌ ፤ – አምርሮ ህሊናው ያዘነው፤ ወጣት የነፃነት ደቀመዝሙር አቶ አንዱዓለም አዝመራውን ከአውድማው ማዬት ጓግቶ ግን …. ምች ሊያጠቃው ዳታ (ዝግመት)ሲፈታተነው መረረው ። መሆንን ያሰተማረን አቶ አንዷለም ይገባዋል። እውነቱንም ነው። ከትናንት ዛሬ እዬተጫነን ጉም እዬለበሰ ሲያዘግም፤ ተስፋው እዬራቀ ሲመጣ …. የፋመው ሲበርደው፤ የጋመው ሲቀዘቅዝ፤ ማግስት ከቅርበት ጋር ሲጣላ፤ ጉድጓድ ውስጥ በቋሳ የተነቀሰ በደል ተሸክሞ ፍዳ ሲከፍል፤ መተንፈሻ ቧንቧው ተጋርዶ አዬር ሲያጣ  - ሲቀረቀርበት፤ ድቅድቅ ባለ እስር ቤት – በተፈነ ጉረኖ ወይንም በረት ሁኖ ያን የመካራ ሌሊት ጋር ለሚያስልፍ የነፃነት ራህብተኛ አርበኛ ጨለማ ነው። ረግረግ ነው። ጨቀጨቅ ነው። ጥቁር ውስጥ ሆኖ ተስፋ አድርጎ እራሱን የሰጠበት ነገር ውሉ ሲላላ … ተስፋው ሲተረተር …. እሳትና ረመጥን ለመረጠ የመሆን ጀግና መርግ ነው ከባድ። ስለሆነም ከቋያው በተወሰነ ደረጃ ትንሽ ራቅ ያለው ቤተሰብ ቀለማሙን የአደራ ቡቃያ ከብክቦ ማሳደግ ግድ ይለዋል …. መልእክቱ ውስጥን ይመረምራል። መንፈሱ ውስጥን ያፋጥጣል። እያንዳንዱ ቃል ውስጥን ይፈታትሻል …. ከራስ ጋር ታርቆ „ሀ“ ብሎ „ሁ“ እንዲቀጥል መባታልን መታጠቅ … ገፋ አድርጎ መሄድን ይጠይቃል። ጫናው ከባድ ቢሆንም ….
እንደ – መሰብሰቢያ
አደራን ተቀብሎ ስለፍትህ የጸናው፤ የቀለጠበት ድርጅት ቢያንስ እውነተኛ ቦታውን እንዳይነሳው …. ስጋቴ ጠርዝ ላይ ነው ያለው … ወድቆ እንዳይፈጠፈጥ እዬሰጋሁ ነው …. እናንተስ ውዶቼ? ያቺ አጋሩም ብቻዋን በአንድ ክንድ አሳር ላይ ያለ ትዳርን ስንቅ በማቀበል፤ ሁሉን ችላ ጽናትን በመቀለብ፤ ታይተው የማይጠገቡ ጮርቃዎች የአባት ናፍቆት እዬቀጣቸው እንዲያድጉ በቀንበጥነታቸው በሄሮድስ መለስ ሰባራ ገል ሌጋሲ ተፈርዶባቸዋል። ደማሞቹ ሁለት ህጻናት ውስጣቸው ያለቅሳል – በናፍቆት ተርመጥምጧል፤ የደጁንም የቤቱንም ሙሉ ኃላፊነት …. የወሰደቸው የነፃነት ትግሉ ዓይነተኛ አካላዊ ክንፍ ባለቤቱም የሰው ህይወትን የመፈወስ የላቀ ሙያዊ ድርሻ፤ የወያኔው እውር ደህንነት አራዊቶች በዬምትንቀሳሰቀስበት ስንዝር የስለላ ጫና … ተሸክማ ያልበላቸውን ዕዳ ስትከፍል በመንፈሱ አንዱ … ያያታል። የማይገፉ ሌሊቶች ካለ መፍትሄ የተፈጥሮን ሂደት ተከትለው ይነጉዳሉ። …  ታዲያ በመራር – የብረት አጥር ኑሮው ከእንቡጦቹ ተለይቶ መኖሩ ላይበቃ የሚቀልጥለት አደራ ቡቃያው ሲጫጫ ውስጡ ተክኖ እንዳይታመም ጠርዝ ላይ ያለው ሌላው የተከደነና እምቅ ስጋቴ ነው …. ማህከነ! አብረን ቆዬን ሳትሰለቹኝ። ኑሩልኝ ታዳሚዎቼ።


እልፍነና እልፍነታችን በተግባር እልፍ እናድርገው።
 ምንጭ፣ http://www.zehabesha.com/amharic/archives/10811

No comments:

Post a Comment